ከነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) የህይወት ታሪክ ስነ ምግባራዊ አስተምህሮት መካከል፡

 ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) በስነ ምግባራቸው ከሰዎች ሁሉ የላቁ ነበሩ

 

ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፣ እጅግ የላቀ ለሆነው የሰው ልጅ መልካም ስነ ምግባር ዓይነተኛ ተምሳሌት ነበሩ፡፡ ቁርኣን የሳቸውን ስነ ምግባር ታላቅ በማለት የገለጸው ለዚህ ነው፡፡ ባለቤታቸው እመት ዓኢሻም(ረ.ዐ) ስለርሳቸው ስነ ምግባር ሲናገሩ፡- ‹‹ስነ ምግባራቸው ቁርኣን ነበር፡፡›› ከማለት ሌላ የተሻለ የረቀቀ አገላላጽ አላገኙለትም፡፡ እርሳቸው፣ ለቁርኣን ስነ ምግባራዊ አስተምሮት ተግባራዊ ተምሳሌት ነበሩ፡፡

 

መተናነስ፡

  • ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) እርሳቸውን በማክበርና በማላቅ አንድም ሰው እንዲቆምላቸው አይፈልጉም ነበር፡፡ ከዚህም አልፎ ሠሐቦቻቸውን እንዲህ ማድረግን ከልክለዋል፡፡ በመሆኑም ሠሐቦች ለርሳቸው ያላቸው ክብርና ውዴታ እጅግ ጠንካራ ከመሆኑ ጋር የእርሳቸውን መምጣት እያዩ አይቆሙላቸውም፡፡ ይህ ሊሆን የቻለው፣ እንዲህ ዓይነቱን ተግባር እርሳቸው እንደሚጠሉ ስላወቁ ነው፡፡ (አህመድ 12345 /አል በዛር 6637)
  • ዐዲይ ቢን ሓቲም(ረ.ዐ) ኢስላምን ሲቀበል፣ ወደርሳቸው ዘንድ መጣ፡፡ ዐዲይ፣ ከዐረብ መኳንንት አንዱ ነበር፡፡ የነብዩን(ሰ.ዐ.ወ) ጥሪ እውነታ ለማወቅ ፈለገ፡፡ ዐዲይ(ረ.ዐ) ይህንን ገጠመኝ ሲናገር፡- «እርሳቸው ዘንድ ስደርስ አንዲት ሴትና አንድ ወይም ከአንድ በላይ ሕፃናት አብረዋቸው ነበሩ፤ - ከነብዩ ጋር ያላቸውን የዝምድና ቅርበትም ጠቅሷል - በዚህን ጊዜ እነሆ እርሱ የኪስራም ሆነ የቀይሠር ንግስና ዓይነት እንዳልሆነ ተረዳሁኝ፡፡» ይላል፡፡ (አህመድ 19381) መተናነስ የነብያት ሁሉ መገለጫ ባህሪ ነው፡፡
  • ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) ከባልደረቦቻቸው ጋር ሲቀመጡ፣ ከነርሱ መካከል እንደሆነ አንድ ተራ ሰው ነበር፡፡ ከነሱ የሚለዩበት ምንም ነገር አይታይባቸውም፡፡ በዙሪያቸው ከሚቀመጡት የሚለያቸው የሆነ ስፍራም አይቀመጡም፡፡ የማያቃቸው እንግዳ ሰው በተቀመጡበት ቦታ በድንገት በሚገባ ጊዜ፣ እርሳቸውን ከባልደረቦቻቸው ለይቶ ማወቅ አይችልም፡፡ እናም «ከመካከላችሁ ሙሐመድ የትኛችሁ ነው? « በማለት ይጠይቅ ነበር፡፡ (አል ቡኻሪ 63)
  • አነስ ቢን ማሊክ እንዲህ ብለዋል፡- «ከመዲና ባሮች መካከል የሆነች አንዲት ባሪያ፣ ጉዳይዋን እንዲያስፈፅሙላት የነቢዩን (ሰ.ዐ.ወ) እጅ ይዛ የፈለገችበት ቦታ ትሄድ ነበር፡፡» (አል ቡኻሪ 5724) ‹‹እጃቸውን ይዛ›› የሚለው ሐረግ፣ ለትንሹም ለደካማውም የነበራቸውን እሺታና ገራገርነት ለመግለፅ የተጠቀሙበት ነው፡፡ ይህ፣ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) በመተናነስ ላይ የነበራቸውን ባህሪ ድካ በደረሰ መልኩ ይገልፃል፡፡ ምክንያቱም በታሪኩ ላይ የተጠቀሰው ወንድ ሳይሆን ሴት፤ ነፃ ሳትሆን ባሪያ ነች፡፡ ከመሆኑም ጋር ጉዳይዋን እንዲያስፈፅሙላት የፈለገችበት ስፍራ ይዛቸው ትሄድ ነበር፡፡
  • ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹በልቡ ውስጥ የቅንጣት ክብደት ያህል ኩራት ያለበት ሰው ጀነት አይገባም፡፡›› (ሙስሊም 91)

እዝነት፡

  • ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፡- ‹‹አዛኞች አርረህማን ያዝንላቸዋል፤ በምድር ውስጥ ላለ እዘኑ፤ ከሰማይ በላይ ያለው ያዝንላችኋልና፡፡›› ብለዋል (አል ቲርሚዚ 1924 / አቡ ዳውድ 4941)

የነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) አዛኝነት በበርካታ ስፍራዎች ላይ ይንጸባረቃል፤ ከነዚህም መካከል፡

ለሕፃናት የነበራቸው እዝነት፡

  • አንድ ገጠሬ ወደ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ዘንድ መጣና፡ «ልጆቻችሁን ትስማላችሁን? እኛ ግን አንስማቸውም፡፡» አላቸው፡፡ ነብዩም (ሰ.ዐ.ወ)፣ ‹‹ታዲያ አላህ ከቀልብህ ውስጥ እዝነትን የነጠቀ ከሆነ እኔ ምን ላደርግልህ እችላለሁ?›› በማለት መልስ ሰጡት፡

(አል ቡኻሪ 5652 ሙስሊም 2317) ሌላ ገጠሬ ደግሞ የዓሊይን ልጅ ሐሰንን ሲስሙ ተመለከታቸውና፣ «እኔ አስር ልጆች አሉኝ ነገር ግን አንዱንም ስሜው አላውቅም፡፡» አለ፡፡ በዚህን ጊዜ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፡- ‹‹እነሆ የማያዝን አይታዘንለትም፡፡›› አሉት፡ (ሙስሊም 2318)

  • አንድ ጊዜ የልጃቸውን ሴት ልጅ፣ ኡማማ ቢንት ዘይነብን ይዘው ሰግደዋል፡፡ ሱጁድ ሲያደርጉ ቁጭ ያደርጓታል፤ ሲቆሙም ይሸከሟት ነበር፡፡ (አል ቡኻሪ 494/ ሙስሊም 543)
  • ሠላት ውስጥ ሆነው የሕፃን ልጅ ለቅሶ ከሰሙ፣ ሠላቱን አጠርና ፈጠን አድርገው ይሰግዱ ነበር፡፡ አቡ ቀታዳ ከነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) የሚከተለውን አስተላልፈዋል፡ ‹‹ሠላት ስሰግድ በውስጧ ማስረዘምን እፈልጋለሁ፤ ከዚያም የሕፃን ልጅ ለቅሶ እሰማለሁ፤ እናም እናትየዋን እንዳላስጨንቃት በማሰብ ሠላቴን አሳጥራለሁ፡፡›› (አል ቡኻሪ 675/ ሙስሊም 470)

ለሴቶች የነበራቸው እዝነት

ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ሴት ልጆችን በመንከባከብ ለነርሱ በጎ በመዋል ላይ አነሳስተዋል፡፡ ‹‹በነዚህ ሴት ልጆች የሆነ ፈተናን የተፈተነ ለነርሱም በጎን የዋለ ሰው ለርሱ ከእሳት ግርዶ ይሆኑለታል፡፡›› ይሉም ነበር፡፡

(አል ቡኻሪ 5649 / ሙስሊም 2629)

የሚስትን መብት በተመለከተ ጠበቅ አድርገዋል፡፡ የሷን ጉዳይ ልዩ ትኩረት ቸረውታል፡፡ የተለየ እንክብካቤም ሰጥተውታል፡፡ ሙስሊሞችም በዚሁ ዙሪያ ከፊላቸው ለከፊሉ አደራን እንዲያስተላልፍ አዘዋል፡፡ ‹‹ ስለ ሴቶች መልካም ነገርን ተናዘዙ፡፡›› ብለዋል፡፡ (አል ቡኻሪ 4890)

ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ከቤተሰባቸው ጋር ገራገር በመሆን ዓይተኛ ተምሳሌት ነበሩ፡፡ ለምሳሌ፣ በአንድ ወቅት ግመላቸው አጠገብ ቁጭ ባሉበት ባለቤታቸው ሠፊያ(ረ.ዐ) እግሯን በጉልበታቸው ላይ በማድረግ ተንጠላጥላ ግመሉ ላይ ወጥታለች፡፡ (አል ቡኻሪ 2120) ልጃቸው ፋጢማ እሳቸው ዘንድ በምትመጣ ጊዜ እጇን ይዘው ይስሟታል፤ እርሳቸው በሚቀመጡበት ቦታም ያስቀምጧታል፡፡ (አቡ ዳውድ 5217)

ለደካሞች የነበራቸው እዝነት

  • ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፣ ሰዎች ወላጅ አልባ ሕፃናትን የመንከባከብ ኃላፊነትን እንዲወስዱ ያነሳሱ ነበር፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፡- አመልካች ጣታቸውንና የመሐል ጣታቸውን በማቆራኘት፣ - ‹‹እኔና ወላጅ አልባ ሕፃንን (የቲምን) የሚንከባከብ ሰው፣ በጀነት ውስጥ እንዲህና እንዲህ ነን›› ብለዋል፡፡ (አል ቡኻሪ 4998)
  • ባሎቻቸው ለሞቱባቸው ሴቶች እና ለችግረኞች ጉዳይ የሚሯሯጥና የሚለፋን ሰው፣ ቀኑን በጾም፣ ሌሊቱን ደግሞ በመስገድ ከሚያሳልፍ፣ በአላህ መንገድ ላይ ከሚታገል ታጋይ ጋር እኩል አድርገውታል፡፡ (አል ቡኻሪ 5661/ ሙስሊም 2982)
  • ለደካሞች መራራትና መደንገጥ፣ መብታቸውን መጠበቅ ወይም መስጠት፣ ለሲሳይ መጨመርና በጠላት ላይ ድልን የመጎናጸፊያ ሰበብም እንደሆነ አስተምረዋል፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፡- ‹‹ደካሞችን ፈልጉልኝ፤ ድልን የምታገኙትም ሆነ ሲሳይን የምታገኙት በደካሞቻችሁ ነው፡፡›› ይላሉ፡፡ (አቡ ዳውድ 2594)

 

ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ለእንሰሳት የነበራቸው እዝነት

  • ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፣ ሰዎች ለእንሰሳት እንዲራሩ ያሳስቡ ነበር፡፡ የማይችሉትን ነገር እንዳያሸክሟቸውና እንዳያንገላቷቸው አስጠንቅቀዋል፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፣ እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹አላህ (ሱ.ወ) በነገሮች ሁሉ አሳምሮ መስራትን ደንግጓል፤ እናም ስትገድሉ አገዳደላችሁን አሳምሩ፤ ስታርዱም አስተራረዳችሁን አሳምሩ፤ አንዳችሁ ቢላዋውን ይሳለው፤ እርዱንም በቶሎ ያሳርፈው ፡፡›› (ሙስሊም 1955)
  • አንድ ሠሐብይ እንዲህ ብሏል፡- በአንድ ወቅት ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ያቃጠልነውን የጉንዳን መንደር ተመለከቱና፣ ‹‹ይሄን ያቃጠለው ማን ነው?›› በማለት ጠየቁ፤ እኛ ነን አልናቸው፤ እሳቸውም፡ ‹‹የእሳት ጌታ እንጂ በእሳት ማንም ማንንም ሊቀጣ አይገባም፡፡›› አሉን፡፡ (አቡ ዳውድ 2675)

ፍትሃዊነት፡

  • ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) የቅርብ ዘመዳቸው ላይም ቢሆን ፍትሃዊውን የአላህ ፍርድ ተፈፃሚ ከማድረግ ወደ ኋላ የሚሉ አልነበሩም፡፡ አላህም እንዲህ ሲል አዟል፡- ‹‹እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በትክክል (በፍትሕ) ቋሚዎች፣ በነፍሶቻችሁ ወይም በወላጆችና በቅርብ ዘመዶች ላይ ቢኾንም እንኳ ለአላህ መስካሪዎች ኹኑ፡፡›› (አል ኒሳእ 135)
  • የተወሰኑ የነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ባልደረቦች፣ ጎሳዋ ውስጥ ክብር የነበራት፣ ሰርቃ የተያዘች አንዲት ሴት ላይ ኢስላማዊው ቅጣት ተፈፃሚ እንዳይሆንባት ለማማለድ ወደ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ዘንድ በመጡ ጊዜ፣ ‹‹የሙሐመድ ነፍስ በእጁ በሆነችው ጌታ እምላለሁ፤ የሙሐመድ ልጅ ፋጢማ ብትስርቅ እንኳን እጇን እቆርጠዋለሁ፡፡›› ብለው መልሰዋቸዋል፡፡ (አል ቡኻሪ 4053 / ሙስሊም 1688)
  • በሰዎች ላይ ወለድ ወይም አራጣ እርም በተደረገ ጊዜ መጀመሪያ የጀመሩት ለርሳቸው እጅግ ቅርብ የሆነውን ሰው በመከልከል ነበር፡፡ ያም አጎታቸው ዐባስ(ረ.ዐ) ነው፡፡ በወቅቱ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹መጀመሪያ ውድቅ የማደርገው የኛን ወለድ ነው፤ የዐባስ ቢን ዐብዱልሙጠሊብን ወለድ (የወለድ ውል ሰርዣለሁ)፤ እነሆ ሁሉም የአራጣ ገንዘብ ውድቅ ሆኗል፡፡›› አሉ፡፡ (ሙስሊም 1218)
  • የአንድ ማኅበረሰብ ዕድገትና ስልጣኔ የሚለካው፣ ደካሞች ምንም ሳይፈሩና ሳያመነቱ ከጉልበተኞች መብታቸውን መውሰድ በመቻላቸው እንደሆነ አስተምረዋል፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹በውስጧ ያሉ ደካሞች ያለ ምንም ፍርሃት መብታቸውን የማይወስዱበት ወይም የማያገኙበት ሕዝብ አይበለጽግም(አይድንም)፡፡›› (ኢብኑ ማጃህ 2426)

በጎ መዋልና ለጋስነት፡

  • ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) በመልካም ነገር ላይ ለጋስ ሰው ነበሩ፡፡ እጅግ በጣም ለጋስ የሚሆኑት ደግሞ በረመዳን ወር፣ ጅብሪል(ዐ.ሰ) በሚጎበኛቸው ጊዜ ነው፡፡ በረመዳን ውስጥ፣ ረመዳን እስከሚያልቅ ድረስ በየሌሊቱ ጅብሪል(ዐ.ሰ) ይጎበኛቸው ነበር፡፡ በዚህም ጉብኝቱ ቁርኣንን ያናብባቸዋል፡፡ እናም ጅብሪል(ዐ.ሰ) በሚጎበኛቸው ጊዜ ለመልካም ነገር ያላቸው ለጋስነት ወይም ፈጣንነት ከተላከ ንፋስ የፈጠነ ነበር፡፡ (አል ቡኻሪ 1803 / ሙስሊም 2308)
  • ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ተጠይቀው ያልሰጡት ነገር የለም፡፡ አንድ ጊዜ፣ የሆነ ሰው ሊጠይቃቸው መጥቶ፣ በሁለት ተራሮች መሐል ያለን ሸለቆ የሚሞሉ ፍየሎችን ሰጡት፤ እናም ሰውየው ወደ ጎሳዎቹ በመመለስ፣ «ሕዝቦቼ ሆይ ስለሙ፤ ሙሐመድ ድህነትን የማይፈራ የሆነን ስጦታን ይሰጣል፡፡» አለ፡፡ (ሙስሊም 2312)
  • በአንድ ወቅትም ሰማንያ ሺህ ዲርሃም መጣላቸውና በከረጢት አስቀመጡት፤ ከዚያም ተመልሰው መጡና አከፋፈሉት፤ አንድንም ለማኝ ሳይመልሱ ሁሉንም አከፋፍለው ጨረሱ፡፡ (አል ሃኪም 5423)
  • አንድ ሰው ወደሳቸው በመምጣት ጠየቃቸውና፡ ‹‹ምንም የምሰጥህ ነገር የለኝም፤ ቢሆንም በኔ ስም ግዛና የሆነ ነገር ከመጣልኝ እከፍለዋለሁ፡፡›› ሲሉት፣ ዑመር(ረ.ዐ) «አንቱ የአላህ መልክተኛ ሆይ፣ አላህ የማይችሉትን ነገር አላስገደደዎትም»- ለምን እራሶዎን ያስጨንቃሉ- ሲላቸው፣ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) የዑመር(ረ.ዐ) አስተያየት አላስደሰታቸውም ነበር፤ ሰውየውም እንዲህ አለ፡ «ስጥ የዙፋኑ ባለቤት እንደሆነ ያሳንስብኛል ብለህ አትፈራ፡፡» አላቸው፤ ነብዩም (ሰ.ዐ.ወ) በሰውየው ንግግር ፈገግ አሉ፡፡ የደስታ ስሜት በፊታቸው ላይ ይንጸባረቅ ነበር፡፡ (አል አሓዲሱል ሙኽታራ 88
  • ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ከሑነይን ዘመቻ በተመለሱ ጊዜ የገጠር ሰዎችና አዲስ ሙስሊሞች ከተገኘው ምርኮ ስጦታ ከጅለው ወደሳቸው መጡ፤ በጣም አጨናነቋቸውም፤ በጣም ከማጨናነቃቸው የተነሳ ወደ ዛፍ ስር አስጠጓቸው፤ የዛፉ ቅርንጫፍ ልብሳቸውን ገፈፋቸው፤ በዚህን ጊዜ ነብዩ(ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ አሉ፡- ‹‹ልብሴን ስጡኝ፤ በነዚህ ዛፎች ቅርንጫፍ ልክ ገንዘብ ቢኖረኝ እንኳን በመካከላችሁ አከፋፍዬው፣ ከዚያም ስስታምም ሆነ ውሸታም፣ እንዲሁም ድህነትን ፈሪ እንዳልሆንኩኝ ታውቁ ነበር፡፡›› አሉ፡፡ (አል ቡኻሪ 2979)

ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፣ የአላህ እዝነትና ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁንና በሁሉም የሕይወት ዘርፎች ውስጥ የመልካም ስነ ምግባር ዓይነተኛ ተምሳሌት ነበሩ፡፡