አንድ ሰው ወደ ኢስላም እንዴት ሊገባ ይችላል?

አንድ ሰው ሁለቱን የእምነት የምስክርነት ቃል ትርጉማቸውን አውቆ፣ በልቦናውም እርግጠኛ ሆኖ፣ በምላሱ በመናዘዝ ወደ ኢስላም ይገባል፡፡ እነኚህ ሁለት የእምነት የምስክርነት ቃሎች የሚከተሉት ናቸው፡

  1. «ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚገዙት አምላክ አለመኖሩን እመሰክራለሁ» ይላል፡፡ ከአላህ ባሻገር በእውነት የሚገዙት አምላክ እንደሌለ በልቦናዬ አምኜ በምላሴ እመሰክራለሁ፤ እርሱን በብቸኝነት አመልካለሁ፤ ለርሱ አጋር የለውም ማለት ነው፡፡
  2. «ሙሐመድ የአላህ መልክተኛ ናቸው ብዬ እመሰክራለሁ» ይላል፡፡ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ)፣ ወደ ሰው ልጆች ሁሉ የተላኩ የአላህ መልክተኛ መሆናቸውን በልቦናዬ አምኜ በምላሴ እመሰክራለሁ፤ ላዘዘው ነገር ታዛዥ፣ ለከለከለውም ተከልካይ እሆናለሁ፤ አላህንም ከርሱ ድንጋጌና ፈለግ ጋር በሚገጥም መልኩ እገዛለሁ፤ ማለት ነው፡፡ (ገጽ፣ 40-48 ተመልከት)

አዲስ ሙስሊም ገላውን ይታጠባል

የሰው ልጅ፣ ወደ ኢስላም የገባበት ቅጽበት በሕይወቱ ውስጥ ከባድ ቦታ ያለው አጋጣሚ ነው፡፡ እውነተኛው ልደቱ ያ ነው፡፡ በሕይወት የመገኘቱን ሚስጥር የሚረዳው ከዚያ በኋላ ነው፡፡ በዚህ ሃይማኖት ውስጥ ከመግባቱ ጋር ተያይዞ ሰውነቱን በጠቅላላ በውሃ መታጠብ ይኖርበታል፡፡ ውስጡን ከማጋራትና ከወንጀሎች እንዳጠራና እንዳጸዳ ሁሉ ላዩንም በውሃ በመታጠብ ቢያጸዳ ይወደድለታል፡፡

ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) አንድ ከዐረብ መኳንንት መካከል የነበረን ሠሐብይ ወደ ኢስላም ለመግባት በፈለገ ጊዜ ሰውነቱን እንዲታጠብ አዘውት ነበር፡፡ (አል በይሃቂ 837)

 ንሠሐ

ንሠሐ፣ ወደ አላህ መመለስ ማለት ነው፡፡ ማንም ሰው ከነበረበት አመጸኝነትና ከሃዲነት ከልቡ በትክክል ወደ አላህ ከተመለሰ ያ ተክክለኛ ንሠሐ ይባላል፡፡

ሙስሊም በእያንዳንዱ የሕይወት እርከን ወደ አላህ መመለስ ወይም ተውባና ምህረትን መለመን ያስፈልገዋል፡፡ የሰው ልጅ በተፈጥሮው ተሳሳች ነው፤ ስለሆነም በተሳሳተ ቁጥር አላህን ምሕረት መለመንና ወደርሱ ንሠሐ መግባት ይኖርበታል፡፡

የትክክለኛ ንሠሐ መስፈርት ምንድነው?

አንድ ሰው፣ ከክህደት፣ በአላህ ከማጋራትና ከሌሎችም ወንጀሎች በሙሉ ተውበት(ንሠሐ) ሲያደርግ፣ ንሠሐው ትክክለኛና ተቀባይነት ያለው እንዲሆን የተወሰኑ ቅድመ መስፈርቶች መሟላት አለባቸው፡፡ ከነዚህ ከቅድመ መስፈርቶች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡

  1. ወንጀሉን ማቆም

ወንጀል እየሰራ ንሠሐ ገብቻለሁ ቢል ንሠሐው ትክክለኛ አይሆንም፡፡ ከትክክለኛ ንሠሐ በኋላ ወደ ወንጀል ቢመለስ፣ ከዚህ በፊት ያሳለፈው ንሠሐ አይበላሽበትም ግን ለሰራው ወንጀል አዲስ ንሠሐ መግባት ያስፈልገዋል፡፡

  1. ላሳለፈው ወንጀል መጸጸትና መቆጨት

ንሠሐ(ተውበት)፣ ከአንድበፈፀመው ወንጀል ከማይጸጸትና በሰራው ሃጢኣት ከማይቆጭ ሰው ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ ያሳለፋቸውን ወንጀሎች የሚያወራን፣ በዚያም ኩራት የሚሰማውንና የሚኮፈስን ሰው ከተጸጻቾች መመደብ አይቻልም፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹ንሠሐ ማለት መጸጸት ነው፡፡›› ( ኢብኑ ማጃህ 4252)

  1. ዳግም ወደ ወንጀሉ ላለመለስ ቁርጠኛ ውሳኔ ማድረግ

ከንሠሐ በኋላ ወደ ነበረበት ወንጀል ለመመለስ የሚያስብ ሰው ንሠሐው ተቀባይነት አይኖረውም፡፡

ውሳኔ ላይ ለመድረስ የሚረዱ እርምጃዎች፡

  • ነፍሱ የትኛውንም ያክል ከባድ ችግር ወይም እንቅፋት ቢገጥማትም ወደ ነበረበት ወንጀል ላለመመለስ ከነፍሱ ጋር ቃል ኪዳን ይገባል፡፡ ነብዩ(ሰ.ዐ.ወ)፡- ‹‹ሦስት ነገሮች በውስጡ የተገኙለት ሰው የኢማንን ጣዕም አግኝቷል፡፡›› ባሉት ንግግራቸው ውስጥ፣ ‹‹አላህ ወደ ኢስላም ከመራው በኋላ ወደ ክህደት መመለስን ልክ እሳት ውስጥ መወርወርን እንደሚጠላው መጥላቱ ነው፡፡›› የሚለውን ጠቅሰዋል፡፡ (አል ቡኻሪ 21/ ሙስሊም 43)
  • ኢማናቸው ከዘቀጠና ወንጀልን ከሚያዘወትሩ ግለሰቦችና ወንጀል ከሚተገበርበት ቦታ መራቅ
  • በገራለት አኳኋንና ቋንቋ አላህን እስከሚሞት ድረስ በሃይማኖቱ ላይ እንዲያጸናው መለመንን ማብዛት አበበት፡፡ ከነዚህም ዱዓዎች መካከል በቁርኣንና በሐዲስ የተጠቀሱ አሉ፡-
    • ‹‹ጌታችን ሆይ ቅኑን መንገድ ከመራኸን በኃላ ልቦቻችንን አታዘምብልብን፤›› (አል ዒምራን 8)
    • ‹‹አንተ ልቦችን ገለባባጭ የሆንክ ጌታ ሆይ ልቤን በእምነት ላይ አጽናው›› (አል ቲርሚዚ 2140)

ከንሠሐ በኋላስ?

አንድ ሰው በትክክል ንሠሐ ከገባና ወደ አላህ ከተመለሰ፣ ወንጀሎቹ ምን የከበዱና የበዙ ቢሆኑም አላህ ወንጀሎቹን በጠቅላላ ይምርለታል፡፡ የአላህ(ሱ.ወ) እዝነት ሁሉን ነገር ያካበበች ነች፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ይላል፡- ‹‹በላቸው፡ እናንተ በነፍሶቻችሁ ላይ ድንበር ያለፋችሁ ባሮቼ ሆይ ከአላህ እዝነት ተስፋ አትቁረጡ፤ አላህ ሃጢአትን በሙሉ ይምራልና፤ እነሆ እርሱ መሃሪው አዛኙ ነውና፡፡›› (አል ዙመር 53)

አንድ ሙስሊም ትክክለኛ ንሠሐ ከገባ በኋላ ወንጀል የሌለበት ንጹሕ ይሆናል፡፡ ከዚህም አልፎ፣ አላህ (ሱ.ወ) እውነተኛ ተጸጻች የሆነን፣ በትክክል መቆጨትን የተቆጨን ንሠሐ አድራጊ ለየት ባለ ታላቅ ካሳ ይክሰዋል፡፡ መጥፎ ሥራዎቹን በበጎ ይቀይርለታል፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፡- ‹‹ተጸጽቶ የተመለሰና ያመነ መልካምም ሥራ የሠራ ሰው ብቻ ሲቀር፤ እነዚያም አላህ መጥፎ ሥራዎቻቸውን በመልካም ሥራዎች ይለውጣል፤ አላህም እጅግ መሐሪ አዛኝ ነው፡፡›› (አል ፉርቃን 70)

በዚህ መልክ የተገለፀ ሰው፣ ይህችን ንሠሐውን በመጠበቅ ላይ ከፍተኛ ጉጉት ሊያድርበት ይገባል፡፡ በሰይጣን ወጥመድ ውስጥ እንዳይገባና ወደ ኋላ እንዳያፈገፍግም የተቻለውን ሁሉ በማድረግ ንሠሐውን መጠበቅ አለበት፡፡

የኢማን ጣዕም ወይም ጥፍጥና

ውዴታው ከማንም በላይ ለአላህና ለመልክተኛው የሆነለት ሰው፣ ሌሎችን የሚወደው ለአላህና ለሃይማኖታቸው ለኢስላም ባላቸው ቀረቤታ ልክ የሆነ፤ ወደነበረበት የክህደትና የማጋራት እንዲሁም የጥመት መንገድ መመለስን ልክ በእሳት መቃጠልን እንደሚጠላ ያክል የጠላ፤ በዚህን ጊዜ በልቡ ውስጥ የኢማንን ጣዕምና ጥፍጥና ያገኛል፡፡ ይህም ከአላህ በሚያገኘው ማበረታቻና እርጋታ፣ በአላህ ድንጋጌዎች በመርካትና በመደሰት፣ እንዲሁም ለቀጥተኛው ጎዳና መመራት ጸጋ ይረጋገጣል፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹ሦስት ነገሮችን በውስጡ ያገኘ ሰው፣ በነርሱ ሰበብ የኢማንን ጣዕም ያገኛል፤ አላህና መልክተኛው ከነርሱ ሌላ ካለ አካል ሁሉ እርሱ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ መሆናቸውን፤ አንድን ሰው ለአላህ ብሎ እንጂ ለሌላ ነገር አለመውደድን፤ አላህ ከርሱ ከገላገለው በኋላ ወደ ክህደት መመለስን ልክ እሳት ውስጥ መወርወርን እንደሚጠላ መጥላትን (በልቡ ውስጥ ያገኘ ሰው፡፡) ›› (አል ቡኻሪ 21 / ሙስሊም 43)

ወደ ቀጥተኛው ጎዳና የመመራትንና የንሠሐን ጸጋ ማመስገን

አንድ ሙስሊም አላህ(ሱ.ወ) በርሱ ላይ ከዋላቸው ጸጋዎች ታላቁ የሆነውን፣ ወደ ቀጥተኛው ጎዳና የመመራትንና የንሠሐን ጸጋ ከሚያመሰግንባቸው መንገዶች ዋና ዋናዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡-

  1. ሃይማኖትን አጥብቆ መያዝና ለሚያጋጥሙ ችግሮች ታጋሽ መሆን

የድልብ ባለቤት የሆነ ሰው፣ ንብረቱ የወሮበሎችና የዘራፊዎች እጅ እንዳያገኘው ከፍተኛ ጥንቃቄና ጥበቃ ያደርግለታል፡፡ ለጉዳት ከሚዳርጉት ነገሮች ሁሉ ይከላከለዋል፡፡ ኢስላም ለሰው ዘር በጠቅላላ የተበረከተ ታላቅ ስጦታ ነው፡፡ የአመለካከት አቅጣጫ ብቻ አይደለም፡፡ ወይም ሰዎች ባሻቸው ጊዜ የሚፈፅሙት ስሜትም አይደለም፡፡ እያንዳንዱን የሕይወት ገጠመኝና እንቅስቃሴ የሚቆጣጠርና የሚያስተዳድር ሃይማኖት ነው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) መልክተኛውን (ሰ.ዐ.ወ) ኢሳላምን፣ የቁርኣንን መመሪያ አጥብቀው እንዲይዙ ያዘዛቸውና በዚህ ጉዳይ ላይ ምንም ዓይነት ማፈግፈግ ሊኖር እንደማይገባ የገለጸላቸው ለዚህ ነው፡፡ ይህም ኢስላም ትክክለኛውና ቀጥተኛው ጎዳና በመሆኑ ነው፡፡

‹‹ያንንም ወዳንተ የተወረደልህን አጥበቀህ ያዝ አንተ በቀጥተኛው መንገድ ላይ ነህና፡፡›› ይላል፡፡ (አል ዙኽሩፍ 43) አንድ ሙስሊም ኢስላምን ከተቀበለ በኋላ በሚያጋጥመው ችግርና መከራ ማዘን የለበትም፡፡ ለችግርና ለመከራ መጋለጥ የአላህ ተፈጥሯዊ ሕግ ነው፡፡ ከኛ በላጭና ታላቅ የነበሩት መልዕክተኛ (ሰ.ዐ.ወ) ብርቱ ችግርና መከራ ደርሶባቸው ታግሰዋል፤ ታግለዋል፡፡ የአላህን ነብያት ብንመለከት፣ አላህ ታሪካቸውን ተርኮልናል፤ በምን መልኩ እንደተንገላቱና እንደተሰቃዩ ነግሮናል፤ ከጠላት በፊት የዘመድና የጓደኛ ጥቃት እንደደረሰባቸው ገልጾልናል፤ ሆኖም በአላህ መንገድ ላይ በገጠማቸው ነገር ምንም አልተዳከሙም፤ የነበራቸውን አቋምና እምነት አልቀየሩም አልለወጡም፡፡ ስለዚህ ይህ በአንተም ላይ የደረሰብህ ችግር፣ እምነትህ እውነተኛ፣ እርግጠኛነትህም ጠንካራ በመሆኑ ከአላህ የሆነ ፈተና ነው፡፡ እናም በፈተናው ልክ አንተም በርታ! ይህን ሃይማኖትህን አጥብቀህ ያዝ፤ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) በዱዓቸው ላይ በብዛት ይደጋግሙ እንደነበረው አንተም አላህን ለምነው፡ ‹‹አንተ ልብን ገለባባጭ የሆንክ ጌታ ሆይ! ልቤን በእምነትህ ላይ አጽናልኝ፡፡›› በል፡፡ (አል ቲርሚዚ 2140) ይህንኑ በማስመልከት አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፡- ‹‹ሰዎች አምነናል በማለታቸው ብቻ እነሱ ሳይፈተኑ የሚተዉ መኾናቸውን ጠረጠሩን? እነዚያንም ከነሱ በፊት የነበሩትን በእርግጥ ፈትነናል፤ እነዚያንም እውነት የተናገሩትን አላህ በእርግጥ ያውቃል፤ ውሸታሞቹንም ያውቃል፡፡›› (አል አንከቡት 2-3)

  1. በጥበብና በመልካም ግሳፄ ወደ ኢስላም በመጣራት ላይ መታገል

ይህ የሰው ልጅ ለተጎናጸፈው የኢስላም ጸጋ ምስጋና ከሚገለፅባቸው መንገዶች መካከል ትልቁ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በአላህ ሃይማኖት ላይ ጽናት እንዲኖር ከሚያደርጉ ምክንያቶችም ዋነኛው ነው፡፡ አንድ ከአደገኛ በሽታ ነፃ የሆነ፣ ሌት ተቀን ሲያንገላታውና ሲያሰቃየው ከነበረው ደዌ ሰውነቱ ጤናማ የሆነለት ሰው፣ እንዲሁም በምን መልኩ ከዚህ በሽታ መገላገያውንና ፍቱን መድሃኒቱን ያወቀ ሰው፣ በሰዎች መሐል ይህን ዕውቀቱን ለማሰራጨት ከፍተኛ ጉጉትና ፍላጎት ያድርበታል፡፡ በተለይም ለቤተሰቦቹ፣ ለቅርብ ዘመዶቹና ለሚወዳቸው ሰዎች ይህን ማስተማሩ ጥርጥር የለውም፡፡ እንግዲህ በሚከተለው መልኩ የሚብራራው ይህ ነው፡፡