ወደ ኢስላም መጣራት

ወደ አላህ መጣራት ያለው ትሩፋት

ወደ አላህ መጣራት ትልቅ ችሮታ ካላቸው ስራዎችና ወደ አላህ ከሚያቃርቡ ነገሮች ላቅ ያለው ነው፡፡ ይህንኑ የሚያደንቁና የሚያበረታቱ የቁርኣን አንቀጾችና የሐዲስ ዘገባዎች አሉ፡፡ ከነዚህም መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡

  1. ወደ አላህ መጣራት በቅርቢቱ ዓለምም ሆነ በወዲያኛው ዓለም የመዳኛና የስኬት መንገድ ነው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፡- ‹‹ከናንተም ወደ በጎ ነገር የሚጠሩ፣ በመልካም ስራም የሚያዙ፣ ከክፉ ነገርም የሚከለክሉ ህዝቦች ይኑሩ፤ እነዚያም እነሱ የሚድኑ ናቸው፡፡›› (አል ዒምራን 104)
  2. የአንድ ወደ ኢስላም ጥሪ አድራጊ ሰው ንግግር አላህ ዘንድ በላጭና ተወዳጅ ነው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) የአንድን ተጣሪ ንግግር ሲያደንቅ እንዲህ ብሏል፡- ‹‹ወደ አላህ ከጠራና መልካምንም ከሰራ፤ እኔ ከሙስሊሞች ነኝ ካለም ሰው ይበልጥ ቃሉ ያማረ ማን ነው?›› (አል ፉሢለት 43) ከርሱ ንግግር የበለጠ ያማረ ንግግር የለም፡፡ ይህ ዓይነቱ ሰው፣ ሰዎች ጌታቸውን፣ ፈጣሪያቸውን፣ እንዲሁም ከማጋራት ጭለማዎች ወደ ኢማን ብርሃን ያወጣቸውን ጌታቸውን እንዲያመልኩ የሚያመለክትና የሚመራ ሰው ነው፡፡
  3. ጥሪ ማድረግ(ዳዕዋ)፣ የአላህን ትዕዛዝ መፈፀምም ነው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ይላል፡- ‹‹ወደ ጌታህ መንገድ በብልሃትና በመልካም ግሳጼ (በለዘብታ ቃል) ጥራ፡፡›› (አል ነሕል 125) ስለሆነም አንድ ተጣሪ ወይም ዳዒ ወደ ኢስላም ሲጣራ በብልሃት ሊሆን ይገባል፡፡ ሁሉንም ነገር በቦታው ማኖር አለበት፡፡ ይኸውም ለሚጠራቸው ወገኖች የሚስማሙና አንገብጋቢ የሆኑ ነገሮችን በመምረጥና በማዘጋጀት እንደየደረጃቸው ምክርና ጣፋጭ የሆነ ተግሳጽን መስጠት ነው፡፡ ለዘብ ባለና ገር በሆነ መልኩ ከነርሱ ጋር መወያየትና ለነርሱ መመራት ቅርብ የሆነውን አካሄድ መጠቀም አለበት፡፡
  4. ወደ አላህ መጣራት የመልክተኞች ሁሉ፣ በተለይ የነቢያችን የሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) ተግባር ነው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እሳቸውን በሰው ልጆች ላይ መስካሪ አድርጓቸዋል፡፡ ለምእመናን በጀነት አብሳሪ፤ ለካሃዲያንና ለአመጸኞች ከእሳት አስጠንቃቂ አድርጎ ልኳቸዋል፡፡ ወደ አላህ የሚጣሩ በሰው ዘር ውስጥ መለኮታዊ ብርሃንን የሚያሰራጩም ናቸው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ይላል፡- ‹‹አንተ ነብይ ሆይ እኛ መስካሪ አብሳሪና አስፈራሪም አድርገን ላክንህ፤ ወደ አላህም በፈቃዱ ጠሪ አብሪ ብርሃንም (አድርገን ላክንህ) አማኞችንም ከአላህ ዘንድ ለነርሱ ታላቅ ችሮታ ያላቸው መኾኑን አብስራቸው፡፡›› (አል አሕዛብ 45-47)
  5. ጥሪ ማድረግ ወይም ዳዕዋ የማይዘጋ የመልካም ነገር በር ነው፡፡ ጥሪህን የተቀበለና በአንተ እጅ የተመራ ሰው ካለ ወይም ከገጠመህ ላንተም የእርሱ ዓይነት ምንዳ አለልህ፡፡ በሠላቱ፣ በአምልኮው፣ ሰዎችን ባስተማረ ቁጥር ላንተም ምንዳው ይጻፍልሃል፡፡ እንዲህ ያለው ተጣሪ የሚያገኘው ጸጋ ምንኛ የላቀ የአላህ ጸጋ ነው፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹ወደ ቀጥተኛው ጎዳና የተጣራ ሰው፣ እርሱን ከነርሱ ምንዳ ምንም ነገር ሳይጎድል የተከተሉት ሰዎች ምንዳ ይጻፍለታል፡፡›› (ሙስሊም 2674)
  6. የአንድ ዳዒ ምንዳ ከዱንያና በውስጧ ካሉ መጣቀሚያ ነገሮች ሁሉ የተሻለና የበለጠ ነው፡፡ አንድ ዳዒ ምንዳውን የሚያገኘው ከአላህ ዘንድ ነው፡፡ ከሰዎች የሚጠብቀው ምንም ዓይነት ምንዳ የለም፡፡ ምንዳው ትልቅ የሚሆነውም ለዚህ ነው፡፡ ለጋሱ አላህ ደግሞ ለሚወደው ትልቅን ነገር እንጂ አይሰጥም፡፡ አላህ (ሱ.ወ) በነቢዩላህ ዩኑስ (ዐ.ሰ) አንደበት እንዲህ ይላል፡- ‹‹ብትሸሹም (አትጎዱኝም) ከምንዳ ምንንም አልለምናችሁምና፡፡ ምንዳዬ በአላህ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም፤ ከሙስሊሞች እንድኾንም ታዝዣለሁ፡፡›› (ዩኑስ 72) ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹አንድን ሰው አላህ በአንተ ሰበብ ቢመራልህ፣ ቀያይ ግመሎች ላንተ ከሚኖሩህ ይሻላል፡፡›› (አል ቡኻሪ 2847 / ሙስሊም 2406)

የትክክለኛ ዳዕዋ(ጥሪ) መገለጫዎች

አላህ(ሱ.ወ)፣ ትክክለኛ ጥሪ ከሌላ የጥሪ ዓይነት የሚለይበትን ባህሪ አብራርቷል፡፡ ትክክለኛ ጥሪ የሚከተሉት መገለጫዎች አሉት፡፡

  1. መረጃና ዕውቀት

አንድ ተጣሪ ወይም ዳዒ ወደርሱ በሚጠራበት ነገር ዕውቀት ሊኖረው ይገባል፡፡ የሚናገረውን ነገር ጠንቅቆ የሚያውቅ መሆን አለበት፡፡ አላህ (ሱ.ወ) ለነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ይላቸዋል፡- ‹‹በል፤ይህች መንገዴ ናት፤ ወደ አላህ እጠራለሁ፤ እኔም የተከተለኝም ሰው በግልጽ ማስረጃ ላይ ነን፡፡›› (ዩሱፍ 108)

አንተ ነብይ ሆይ! መንገዴ፣ መመሪያዬ ይህ ነው፤ በዕውቀትና በመረጃ ላይ ተመስርቶ ወደ አላህ መጣራት ነው፤ ይህ ደግሞ እኔን የተከተሉ ተጣሪዎችም መንገድ ነው ብለህ ግለጽ እያላቸው ነው፡፡

አንድ ተጣሪ ወደ አላህ መንገድ ለማጣራት የግድ በርካታ ነገሮችን ማወቅ አይጠበቅበትም፡፡ አንድን ሸሪዓዊ ሕግ ካወቀ ወደዚያ ነገር የመጣራት ኃላፊነት ይኖርበታል፡፡ አላህን በብቸኝነት መገዛትን (ተውሒድን) ከተማረ፣ ይህንኑ ለሰዎች የማድረስ ግዴታ ይኖርበታል፡፡ የኢስላምን መልካምነት ካወቀ ያወቀውን ያክል ለሰዎች ማስተላለፍ አለበት፡፡ የሚያውቀው አንዲትን የቁርኣን አንቀጽ ቢሆንም እንኳን ለሰዎች የማድረስ ግዴታ ይኖርበታል፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡- ‹‹አንዲት አንቀጽ ብትሆንም ከኔ የሰማችሁትን አስተላልፉ፡›› (አል ቡኻሪ 3274) ሠሓቦችም እንዲሁ ነበሩ፡፡ ወደ ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) ዘንድ በመምጣት ኢስላምን ይቀበሉና በትንሽ ቀናት ውስጥ የሃይማኖቱን መሰረታዊ መርሆችንና መመሪያዎችን ይማራሉ፤ ከዚያም ወደ ጎሳዎቻቸው በመመለስ ወደ ኢስላም ጥሪ ያደርጋሉ፤ እንዲሰልሙ ያነሳሱዋቸዋል፡፡ ባህሪያቸው፣ ሰዎች ኢስላምን እንዲወዱና እንዲቀበሉ የሚጋብዝና የሚያበረታታ ነበር፡፡

  1. በዳዕዋ ውስጥ ብልሃትን መጠቀም

አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ይላል፡- ‹‹ወደ ጌታህ መንገድ በብልሃትና በመልካም ግሳጼ (በለዘብታ ቃል) ጥራ፤ በዚያችም እርሷ መልካም በኾነችው (ዘዴ) ተከራከራቸው፡፡›› (አል ነሕል 125)

ብልሃት ማለት፡ መስራት የሚገባን ነገር በሚጣጣም መልኩ መስራትና ከሚሰራው ስራ ጋር የሚስማማ የሆነን ጊዜና ቦታን መምረጥ ነው፡፡

የሰዎች ዝንባሌና ወደ ልባቸው የመግቢያ መንገድ የተለያየ ነው፡፡ ነገርን የመረዳትና የመገንዘብ ችሎታቸውም አንድ ዓይነት አይደለም፡፡ ስለሆነም ዳዕዋ አድራጊ ሰው ለእያንዳንዱ ሰው የሚስማማ የሆነን ዘዴ መጠቀም ይኖርበታል፡፡ እጅግ በጣም ጫና ሊያሳድሩ የሚችሉ የሕይወት ገጠመኞችን ሊጠባበቅና ለዳዕዋ አመቺ በሆነ መልኩ ሊጠቀምባቸው ይገባል፡፡

የሰዎች ዝንባሌና ወደ ልባቸው የመግቢያ መንገድ የተለያየ ነው፡፡  ነገርን የመረዳትና የመገንዘብ ችሎታቸውም አንድ ዓይነት አይደለም፡፡ ስለሆነም ዳዕዋ አድራጊ ሰው ለእያንዳንዱ ሰው የሚስማማ የሆነን ዘዴ መጠቀም ይኖርበታል፡፡ እጅግ በጣም ጫና ሊያሳድሩ የሚችሉ የሕይወት ገጠመኞችን ሊጠባበቅና ለዳዕዋ አመቺ በሆነ መልኩ ሊጠቀምባቸው ይገባል፡፡

ዳዕዋ ለሚያደርግላቸው ሰዎች ምንጊዜም ገርነትን፣ መልካም ግሳጼንና እዝነትን ማንጸባረቅ ይኖርበታል፡፡ እልህና ንትርክ ውስጥ የማይከት የሆነ ረጋ ያለ ውይይት ማካሄድም አስፈላጊ ነው፡፡  አላህ (ሱ.ወ) ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ከሰዎች ጋር የነበራቸውን ገርነትና ይቅር ባይነት በአድናቆት ያወሳው ሲሆን፣ ልበ ደረቅ፣ ጨካኝ ቢሆኑ ኖሮ በዙሪያቸው የነበሩት ትተዋቸው ይበተኑ እንደነበረም አስጠንቅቋል፡፡ እንዲህም ይላል፡- 

‹‹ከአላህም በሆነ ችሮታ ለዘብክላቸው፤ዐመለ መጥፎ ልበ ደረቅም በሆንክ ኖሮ ከዙሪያህ በተበተኑ ነበር፡፡››  (አል ዒምራን 159)

ቤተሰብን መጣራት

አላህ ኢስላምን እንዲቀበል የቸረው ሰው፣ ቤተሰቦቹንና የቅርብ ዘመዶቹን ወደ ኢስላም የመጥራት ከፍተኛ ጉጉት ሊያድርበት ይገባል፡፡ ምክንያቱም እነርሱ ከማንም በላይ ለርሱ ቅርቦቹና ወዳጆቹም በመሆናቸው ነው፡፡ ለዚህም ከነርሱ የሚደርስበትን ስቃይና እንግልት በትግስት ማሳለፍ አለበት፡፡ የተለያዩ በብልሃት የተሞሉ መንገዶችን መጠቀም ይኖርበታል፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ይላል፡-

‹‹ቤተሰብህንም በስግደት እዘዝ፤ በርሷም ላይ ዘውትር፡፡›› (ጧሃ 132) አንዳንድ ሰዎች በሚያደርጉት ዳዕዋ ባዕድ ሲቀበላቸው ቤተሰባቸውና የቅርብ ዘመዳቸው ግን እንቢተኛ ሲሆን እንመለከታለን፡፡ በዚህም እጅግ ይበሳጫሉ፤ ተስፋም ይቆርጣሉ፡፡ ነገር ግን ስኬታማ ዳዕዋ አድራጊ፣ የዳዕዋ ስልቶችንና አካሄዶችን በመቀያየር በተለያየ መንገድ ዳዕዋ በማድረግ የሚታገልና ዳዕዋ ለሚያደርግላቸው ሰዎች አላህ(ሱ.ወ) እንዲመራቸው የሚማጸንላቸው የሆነ ሰው ነው፡፡ እልህ አስጨራሽ በሆኑ አጋጣሚዎች ላይም ተስፋ አይቆርጥም፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ) ከአጎታቸው አቡ ጣሊብ ጋር የነበራቸውን ታሪክ ብንመለከት፣ አጎታቸው ይረዳቸው፣ ይደግፋቸው፣ ከቁረይሾችም ጥቃት ይከላከልላቸው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ኢስላምን አልተቀበለም፤ ነብዩም (ሰ.ዐ.ወ) እርሱን ወደ ኢስላም በመጥራት የሚያደርጉትን ሙከራ እስከመጨረሻው እስትንፋሱ ድረስ አላቋረጡም፡፡ በዚያ ቅጽበት ላይ ሆኖ፡- ‹‹አጎቴ ሆይ ላኢላሃ ኢለላህ በል፤ አላህ ዘንድ የምሞግትልህ የሆነችን ቃል በል፡፡›› አሉት፡፡ (አል ቡኻሪ 3671/ ሙስሊም 24) ነገር ግን ለርሳቸው ጥሪ ምላሽ ሳይሰጥ በክህደት ላይ ሞተ፤ አላህም የሚከተለውን አንቀጽ አወረደ፤ ‹‹አንተ የወደድከውን ሰው ፈጽሞ አታቀናም፤ ግን አላህ የሚሻውን ሰው ያቀናል፤ እርሱም ቅኖቹን ዐዋቂ ነው፡፡›› (አል ቀሠሥ 56 ) አንድ ዳዕዋ የሚያደርግ ሰው የሚቻለውን ሁሉ በማድረግ ሃይማኖቱን የማሰራጨትና ሰዎችን ወደ መልካም ነገር የመምራት ግዴታ አለበት፡፡ ልቦች በአላህ እጅ ናቸው፤ የሻውን ወደ ቀጥተኛው መንገድ ይመራል፡፡